"በውድድሩ ያሳያችሁት ብቃት ካለፈው የተሻለ በመሆኑ በቀጣይ ጠንክረን ከሰራን የተሻለ ውጤት ማስመዝገብ እንደምንችል ተገንዝበናል" ክቡር ኮሚሽነር ጀነራል ደመላሽ ገ/ሚካኤል

አዲስ አበባ፣ የካቲት 5 ቀን 2018 ዓ.ም (ኢ.ፌ.ፖ.ሚ) የኢትዮጵያ ፌደራል ፖሊስ አዛዥ ክቡር ኮሚሽነር ጀነራል ደመላሽ ገ/ሚካኤል በውድድሩ ያሳያችሁት ብቃት ካለፈው የተሻለ በመሆኑ በቀጣይ ጠንክረን ከሰራን የተሻለ ውጤት ማስመዝገብ እንደምንችል ተገንዝበናል ያሉት ለSWAT TEAM በተደረገው አቀባበል ላይ ነው፡፡

photo_2026-02-13_15-13-55_1770984874.jpg

ክቡር ኮሚሽነር ጀነራል ለSWAT TEAM በሰጡት የሥራ መመሪያ የሀገራችን ህዝብ የለመደው በውድድር መሳተፍን ብቻ ሳይሆን ሁሌም በአሸናፊነት ማጠናቀቅን በመሆኑ በቀጣይ ከምናደርገው ተሳትፎ ባለፈ የተሻለ ውጤት በማስመዝገብ የሀገራችንን ሰንደቅ ዓላማ በዓለም አደባባይ ከፍ በማድረግ የመጀመሪያዎቹን ደረጃ ለመያዝ መዘጋጀት አለብን ብለዋል። 

በውድድሩ ወቅት የነበሩ ስኬቶችና እጥረቶችን በግልጽ በመለየት፤ ለውድድሩ የሚያስፈልጉ ኢንፍራስትራክቸር እና ትጥቆችን በማሟላት፣ የተወዳዳሪውን ቁጥር ከአንድ ወደ ሁለት ቲም ለማሳደግ ለውድድሩ የሚሆኑ አቅም ያላቸውን መልምሎ በስልጠና በማብቃት በሚቀጥለው ውድድር ከምርጥ ቡድኖች መካከል ለመግባት ከወዲሁ መዘጋጀት ያስፈልጋል ብለዋል ክቡር ኮሚሽነር ጀነራል፡፡

በመርሃ ግብሩ ላይ የተሳተፉት የማኔጅመንት አባላትም እንደ ፖሊስ ሌሎች አዳዲስ ነገሮችን ሠርተን ለዓለም እያስተዋወቅን እንዳለን ሁሉ በ 'SWAT Challenge' ውድድርም ካለፉት ውድድሮች ልምድ ወስደን እና የሚያስፈልጉንን ትጥቆች አሟልተን በተሻለ ዝግጅት ብቁ ተወዳዳሪ መሆን እንድንችል የኢትዮጵያ ፖሊስ ዩኒቨርሲቲ ኃላፊነቱን ወስዶ ጠንካራና ተከታታይነት ያለው ሥልጠና መስጠት አለበት ሲሉ ተናግረዋል።

የታተመበት ቀን:-2026-02-11
ተጨማሪ ዜናዎች