የኮሚሽነር ጄኔራል መልዕክት

photo_2022-03-30_17-55-54 (2)_1650961997.jpg

ይህንን ለውጥ ከግብ ለማድረስ የህግ የበላይነትን በማረጋገጥ ዜጎች ያለ ምንም የጸጥታ ስጋት የዕለት ተዕለት ኑሯቸውን እንዲመሩ ማስቻል ወሳኝ ነው፡፡ የኢትዮጵያ ፌደራል ፖሊስ በህግ የተሰጠውን ወንጀልን በመከላከል የህዝብን ሠላምና ደህንነት የማረጋገጥ ተልዕኮና ኃላፊነት በብቃት ለመወጣት ህገ-መንግስቱንና ሌሎች ህጎችን ለመጠበቅ ከመቼውም ጊዜ በላይ በተሻለ ቁመና ላይ ይገኛል።

የህግ የበላይነትን በማረጋገጥ አስተማማኝ ሰላምን ለማስፈን የሕዝብን ደህንነት ማስከበር የተቋሙን ዋነኛ ተግባር መሆኑ ይታወቃል። ይህን ተግባር ከግብ ለማድረስ ተቋማችን ከህዝብ ጋር የበለጠ ተቀራርቦ ለመስራት ዝግጁ ነው።

ከኢትዮጵያ ብሄሮች፣ ብሄረሰቦችና ህዝቦች መሠረታዊ ዓላማዎች ውስጥ አንዱ የሆነው በሕግ የበላይነት ላይ የተመሠረተ አንድ የፖለቲካ ማህበረሰብ በጋራ የመገንባት ዓላማ ከግብ የሚደርሰው የግለሰብና የቡድን መሠረታዊ መብቶችና ነፃነቶች መከበራቸው ሲረጋገጥ ነው።

በተለይ ከቅርብ ጊዜ ወዲህ በሀገራችን በተለያዩ አካባቢዎች አቅደው ግጭቶችን በመቀስቀስ ለዜጎች ሞት፣ መፈናቀል፣ ከፍተኛ የንብረት ጉዳት እና የሰብዓዊ መብት ጥሰት እያደረሱ የሚገኙ አካላትን የሕግ የበላይነትና የህዝባችንን ደኅንነት ለማረጋገጥ ሲባል የጸጥታ ኃይላችን ጠንከር ያለ ህጋዊ እርምጃ በመውሰድ እነዚህን መብቶችና ነፃነቶች በማስከበርና በማክበር ድርሻውን እየተወጣ ይገኛል።

ተቋሙ የህግ የበላይነትን ለማስከበር ወንጀል ከመፈፀሙ በፊት በጥናትና ምርምር፣ ከአዝማሚያ ትንተና እና ከህዝብ አስተያየት በመነሳት ሊፈፀሙ የሚችሉ ወንጀሎችን በማምከን የቅድመ መከላከል ስራ ይሰራል። ከዚህ አልፎ ወንጀል ከተፈፀመ የወንጀል ድርጊቱን በማጣራት ማስረጃ በማሰባሰብ በጥፋተኞች ላይ ህጋዊ እርምጃ እንዲወሰድ ከአቃቤ ህግ አካላት ጋር በመተባበር እስከ መጨረሻው ጉዳዩን በመከታተል ፍርድ እንዲሰጥ ያደርጋል።

በህዝባችን ትግልና ግፊት የመጣው ለውጥ ሀገራችንን ወደ ዲሞክራሲያዊ ሥርዓት የሚያሸጋግር፣ ለሀገራችን ዘላቂ ብልጽግና መሠረት የሚጥል፣ የዜጎች መሠረታዊ ሰብዓዊ መብቶች እንዲከበሩ እና ህዝባችን በተቋሙ ላይ የሚያነሳቸውን ቅሬታዎች ለመፍታት የማይቋረጥ ቋሚ የአሰራር ሥርዓትና የአደረጃጀት ለውጥ የተደረገ ሲሆን በቀጣይም ተቋሙ ከህዝባችንና ከባለድርሻ አካላት ጋር በመሆን የኢኮኖሚ አሻጥር ፣ ሙስናንና ሌብነት፣ የሰብዓዊ መብት ጥሰት ወዘተ… ላይ የተሳተፉ የህገ ወጦችን ወደ ህግ የማቅረቡ ስራ ተጠናክሮ ይቀጥላል።

ተቋሙ የሀገራችንን ህግና ስርዓት በማያከብሩና ጥፋት የሚፈጽሙ አካላትን የማይታገስና ለድርድር የማያቀርብ ነው።

ለተቋሙ በህገ-መንግስቱና በሌሎች ህጎች ተለይተው የተሰጡትን፤ ዝርዝር ተልዕኮዎችና ተግባራት በስኬት ለመወጣት በመረጃ ላይ ተመሰረተ የፖሊስ አገልግሎት በመስጠት መላው ህዝባችንን በማሕበረሰብ አቀፍ የፖሊስ አገልግሎት (Community Policing) መርህ ከጎናችን አሰልፈን ሙስናና፤ ሌብነት፣ እንዲሁም የሰብዓዊ መብት ጥሰት እንዳይፈፀም እየተዋጋን፣ ዘመናዊ ፖሊሳዊ እውቀትና ክህሎት የሚያስጨብጡንን ልምዶችና ተሞክሮዎችን በመቀመርና በማሳደግ፣ በመልካም ሙያዊ ዲስኘሊንና ስነ-ምግባር ታንጸን ተልዕኮዎቻችንን በብቃት እንወጣለን።

ወንጀልን በመከላከልና ሽብርተኝነትን በመዋጋት ተልዕኮዎቻችንን ለመወጣት በምናደርገው ጥረት የሀገራችን ህዝቦች ዛሬም እንደወትሮው ሁሉ ከጎናችን እንዲሰለፉ ጥሪዬን እያስተላለፍኩ ከህዝባችን ጋር እጅ ለእጅ ተያይዘን ሀገራችን ኢትዮጵያ በጀመረችውን የውጥ ጉዞ ሁሉ ከኛ የሚጠበቀውን አስተዋፅኦ ለማበርከት ጠንክረን እንደምንሠራ ያለኝን ፅኑ እምነት ለማረጋገጥ እወዳለሁ፡፡  

በመጨረሻም የኢትዮጵያ ፌደራለ ፖሊስ ከህዝብ ዘንድ ለመድረስ የሁለትዮሽ ተግባቦት ዘዴ /Two way communication/ በመጠቀም በየጊዜው የሚወስዳቸው ህጋዊ እርምጃዎችንና ሌሎች ወቅታዊና ትክክለኛ መረጃ በቀጣይነት ለህዝባችን ተደራሽ ለማድረግ እንዲችል ይህ ድረ-ገፅ ሥራ መጀመሩን እያበሰርኩ በዚህ ድረ-ገፅ በስራችን ላይ ያላችሁን ማንኛውንም አስተያየትና ጥቆማ በማድረስ የጸካ የመረጃ ልውውጥ እንደሚኖረን ተስፋ አደርጋለሁ። አመሰግናለሁ። መልካም የስራ ጊዜ ይሁንልን።

በጀግንነት መጠበቅ በሰብዓዊነት ማገልገል!

 

ደመላሽ ገብረሚካኤል

የኢትዮጵያ ፌደራል ፖሊስ ኮሚሽነር ጀነራል

©2015