የኢትዮጵያ ፌደራል ፖሊስ የህጻናት ማቆያ አስመርቆ ሥራ አስጀመረ

አዲስ አበባ፣ ሐምሌ 06 ቀን 2015 ዓ.ም (ኢፌፖሚ)፡-የኢትዮጵያ ፌደራል ፖሊስ የህፃናት ማቆያ (ዴይ ኬር) በወንጀል ምርመራ ጠቅላይ መምሪያ ቅጥር ግቢ አስመርቆ ሥራ አስጀመረ፡፡

በምረቃ ስነ ስርዓቱ ላይ ተገኝተው መልእክት ያስተላለፉት ክቡር የኢትዮጵያ ፌደራል ፖሊስ ኮሚሽነር ጀነራል ደመላሽ ገ/ሚካኤል የወቅቱ የምስራቅ አፍሪካ ፖሊስ አዛዦች ኅብረት ድርጅት ፕሬዚዳንት በህፃናት ማቆያ ህፃናቶቻችንን ስናቆይ ከሁሉም የፖሊስ ቤተሰብ ጋር እየተገናኙ አብሮ የሚያድጉ በመሆኑ የተሻለ ጠንካራ የፖሊስ ቤተሰብ ከመፍጠሩም ባሻገር ነገ ለምናስባት ኢትዮጵያ መሠረት የሚጥል ስለሆነ ሥራው በስፋት ተጠናክሮ እንደሚቀጥል ገልፀዋል።

የወንጀል ምርመራ ጠቅላይ መምሪያ ከሌሎች ሥራዎች ጎን ለጎን የህፃናት ማቆያዉ እንዲሰራ ማድረጉ መልካም አርዓያ መሆኑን ተናግረው አሁን እያስቸገረን ያለዉን በብሔር፣ በሀይማኖት እና በፖለቲካ የሚፈጠሩ ልዩነቶችን ማጥበብ የሚቻለው እና ነገ የተሻለች ኢትዮጵያን ለማየት ዛሬ በልጆቻችን ላይ ስንሰራ መሆኑን ተናግረዋል ።

ሁሉም ጠቅላይ መምሪያዎች በቀጣይ ከዚህ ተሞክሮ ወስደው የራሳቸው የህፃናት ማቆያ ማዕከላት እንዲኖራቸው በማድረግ የሴት ፖሊስ አመራር እና አባላት ልጆቻቸውን በቅርበት እየተከታተሉ ሥራቸውን በነፃነት መስራት እንዲችሉ ማድረግ ይኖርባቸዋል ብለዋል።

Image4_1689323828.jpg

የኢትዮጵያ ፖሊስ እያመጣ ያለውን ለዉጥ በሁሉም መስክ አጠናክረን በመቀጠል የሠራዊቱን ህይወት የሚቀይሩ መሠረታዊ የሆኑ ጉዳዮችን ለመፍታት ከመንግሥት ጋር በቅርበት እየተሰራ መሆኑን ገልፀው የህፃናት ማቆያዉ ለአገልግሎት እንዲበቃ ላደረጉ አካላት በራሳቸውና በተቋሙ ስም ምስጋና አቅርበዋል።

የኢትዮጵያ ፌደራል ፖሊስ የሴቶችና ሕፃናት ጉዳይ መምሪያ ኃላፊ ክብርት ረዳት ኮሚሽነር ሳዲያ አብዱሮ በበኩላቸው ባደረጉት ንግግር ሴቶች ልጆቻቸዉን በሚሰሩበት አካባቢ የሚያቆዩበትና ጡት የሚያጠቡበት ሁኔታ ማመቻቸት ተገቢ ስለሆነ ሴቶች በመዉለዳችዉ ምክንያት በሥራችዉ ዉጤታማ እንዳይሆኑ ይፈጠርባችዉ የነበረዉን ጫና በመቀነስ ዕዉቀታችዉን፣ ሙሉ ኃይላችዉን እና ጉልበታችዉን ያለምንም ስጋትና ሃሳብ በወንጀል መከላከል ሥራ ላይ እንዲያዉሉ ማድረግ ያስፈልጋል ብለዋል።

የኢትዮጵያ ፌደራል ፖሊስ ከ2011 ዓ.ም ጀምሮ የህፃናት ማቆያ ለመስራት ከመንግስት የወረደውን መመሪያ ተቀብሎ ወደ ተግባር ለመግባት በርካታ እንቅስቃሴዎችን ሲያደርግ መቆየቱንና በአሁኑ ወቅት የተቋሙ አመራሮች በሰጡት ከፍተኛ ትኩረት አስፈላጊዉ በጀት ተመድቦ የህፃናት ማቆያዉ አገልግሎት እንዲሰጥ በመደረጉ በተቋሙ ያሉ ሴት አመራሮችና አባሎች በሥራ ላይ ያላቸዉን ተሳትፎ የበለጠ እንዲያሳድጉ እና እራሳችዉን እያበቁ ወደ አመራርነት እንዲመጡ ለማድረግ ከፍተኛ ጠቀሜታ እንዳለው ክብርት ረዳት ኮሚሽነር ገልፀዋል፡፡

በምረቃው ሥነ-ስርዓት ላይ ምክትል ኮሚሽነር ጀነራሎች፣ የኢ.ፌ.ዲ.ሪ የሴቶችና ማህበራዊ ጉዳይ ሚኒስቴር የሴቶችና ህፃናት ዘርፍ ሚኒስትር ዴኤታ ክብርት ወ/ሮ አለሚቱ ኡሞድ እና የፖሊስ ኮሚሽነሮች እንዲሁም ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶች ተገኝተዋል።

የታተመበት ቀን:-2023-07-13
ተጨማሪ ዜናዎች