በሕገ-ወጥ መንገድ ከ5 ቢሊየን ብር በላይ ሲያንቀሳቅስ የነበረ ግለሰብ በቁጥጥር ስር መዋሉ ተገለፀ
አዲስ አበባ፣ ጥቅምት 16 ቀን 2015 ዓ.ም (ኢፌፖሚ) የኢትዮጵያ ፌደራል ፖሊስ ከኅብረተሰቡ በደረሰው ጥቆማና ባደረገው ብርቱ ክትትል በህገ-ወጥ መንገድ መንገድ ከ5 ነጥብ 1 ቢሊዮን ብር (ከአምስት ነጥብ አንድ ቢሊዮን ብር) በላይ ሲያንቀሳቅስ የነበረ ግለሰብ ከ25 ግብረ-አበሮቹ ጋር የገንዘብ ልውውጥ ያደርግ መሆኑ አረጋግጦ በቁጥጥር ስር አውሎ ምርመራ እያጣራበት መሆኑን ገለፀ፡፡
በወንጀሉ የተጠረጠረው ሳሙኤል እጓለ አለሙ በቅፅል ስሙ ሳሚ ዶላር የሚባል ሲሆን ነዋሪነቱን በአዲስ አበባ ከተማ በማድረግ ወደ አሜሪካን ሀገር በተደጋጋሚ የሚመላለስ የኤሌክትሪክ መሳሪያዎች፣ የቤት እና የቢሮ እቃዎች እንዲሁም ተዛማጅ መገልገያዎች የችርቻሮ ንግድ ፍቃድን ሽፋን በማድረግ ሕገ-ወጥ የውጭ ምንዛሬና በሕገ-ወጥ የገንዘብ ዝውውር ወንጀል ተጠርጥሮ በራሱና ዮዲት እጓለ አለሙ ከተባለች እህቱ ጋር በመሆን በስማቸው በተለያዩ ባንኮች በከፈቷቸው ሃያ አምስት የባንክ አካውንቶች በአንድ ዓመት ውስጥ ከ247 ሚሊየን ብር (ሁለት መቶ አርባ ሰባት ሚሊየን ብር) በላይ ማንቀሳቀሳቸውን ፖሊስ ደርሶባቸው ምርመራ እየተጣራባቸው መሆኑ ታውቋል፡፡

ከዚህ በተጨማሪም ግለሰቡ ከሃያ አምስቱ የወንጀል ግብረ-አበሮቹ ጋር በመሆን በህገ-ወጥ መንገድ ከ5 ነጥብ 1 ቢሊዮን ብር (ከአምስት ነጥብ አንድ ቢሊዮን ብር) በላይ ሲያንቀሳቅሱ እንደነበር በቅድመ ምርመራ ተደርሶባቸዋል፡፡
ተጠርጣሪዎቹ በሕገ-ወጥ የውጭ ሀገር የገንዘብ ዝውውር፣ በግብር ስወራ ወንጀል እና ከህወሃት የሽብር ቡድን ጋር የግንኙነት መረብ በመፍጠር ከፍተኛ ገንዘብ ሲያዘዋውሩ እንደነበር ተጠርጥረው ምርመራ እየተካሄደባቸው ይገኛል፡፡
ተጠርጣሪዎቹ በአጠቃላይ በአንድ ዓመት ውስጥ 5,248,000,000 (አምስት ቢሊዮን ሁለት መቶ አርባ ስምንት ሚሊየን ብር) በላይ በሕገ-ወጥ መንገድ ሲያንቀሳቅሱ እንደነበር ፖሊስ ባደረገው ምርመራ ደርሶባቸዋል።
በመጨረሻም ተጠርጣሪዎቹ በቁጥጥር ሥር እንዲውሉ ኅብረተሰቡ ላደረገው ቀና ትብብር ተቋሙ ላቅ ያለ ምስጋና እያቀረበ ተመሳሳይ የወንጀል ድርጊት ሲያጋጥም በአፋጣኝ በስልክ ቁጥሮች 0115 30 91 39፣ 0111 11 94 75፣ 0111 71 10 12 እንዲሁም 816 ነፃ የስልክ መስመር በመጠቀም ጥቆማ በመስጠት የተለመደ ድጋፍና ትብብር እንዲያደርግ ጥሪውን ያስተላልፋል።
የታተመበት ቀን:-2022-10-25